Monday, December 22, 2014

ቶም እና ጄሪ

By Daniel Kibret

«ቶም እና ጄሪ» ፊልም ዊልያም ሐና እና ዮሴፍ ባርባራ በተባሉ ባለሞያዎች ለሜትሮ ጎልድዊን ካምፓኒ የተሠራ ተከታታይ የካርቱን ፊልም ነው፡፡ የቤት ውስጥ ድመት በሆነው በቶም እና በተንኮለኛዋ አይጥ በጄሪ መካከል በማያቋርጥ ቅንቃኔ እና ጠላትነት እየተቀጣጠለ የሚሄደው ይሄ ፊልም፣ አስገራሚም አስቂኝም ነው፡፡ 

በ1940 እኤአ የተጀመረው ቶም እና ጄሪ፣የአኒሜሽኑ ኩባንያ እስከ ተዘጋበት እስከ 1957 እኤአ ብቻ 114 ያህል ተከታታይ ፊልሞችን በሐና እና በባርባራ ደራሲነት እና አዘጋጅነት አቅርቧል፡፡

በ1960 እኤአ በአዲስ መልክ ፊልሙ እንደ ገና መዘጋጀት እና መታየት ጀመረ፡፡ ዛሬ በታይም ዋርነር ካምፓኒ ባለቤትነት እና በዋርነር ብሮስ አከፋፋይነት የተያዘው የቶም እና ጄሪ የካርቱን ፊልም 162 ተከታታይ ፊልሞችን ያጠቃልላል፡፡

ቶም እና ጄሪ አብረው በአንድ ሰው ቤት ውስጥ የሚኖሩ ነገር ግን መቼም ቢሆን ተስማምተው የማያውቁ ፍጡራን ናቸው፡፡ አልፎ አልፎ በጥቅም ምክንያት ሲስማሙ እንኳን በአከፋፈሉ ምክንያት ለመጣላት ጊዜ አይወስድባቸውም፡፡ ሁለቱንም የሚቃረን ነገር ከመጣ ግንባር የሚፈጥሩት ቶም እና ጄሪ፣ የጋራ ጠላታቸውን ለየራሳቸው ምክንያት ሲሉ ካጠቁ በኋላ እንደገና እርስ በርሳቸው መጣላት ይቀጥላሉ፡፡


ይህ፣ መቼም የማያባራ የቶም እና የጄሪ የቅንቃኔ እና የጠላትነት ፊልም፣ በባለቤቶቹ ዘንድ የታወቁ 162 ተከታታይ ፊልሞች አሉት ቢባልም ጠቅላላ የፊልሞቹ ብዛት ግን ከዚህ ሳይበልጥ አይቀርም፡፡ ለምሳሌ 163ኛው ፊልም የሚዘጋጀውም፣ የሚሠራውም፣ የሚቀርበውም እኛው ሀገር ነው፡፡ ፊልሙን የደረሱትም፣ የሚያዘጋጁትም፣ የሚተውኑትም የ1960ዎቹ የኢትዮጵያ ትውልዶች ናቸው፡

Friday, December 19, 2014

መመረሽ፣መፈረሽ፣መደንበሽ



መጀመርያ ወደ ሱዳን ኤምባሲ ሄዳችሁ ሱዳን የመግቢያ ቪዛ ታወጣላችሁ፡፡ ከዚያ በጎንደር በመተማ በኩል ወደ ሱዳን ትገሠግሣላችሁ፡፡ ‘የሱዳን ሕዝብ ጥሩ ነው፣ለስደተኞች ይራራል‘ ይላሉ ጣልያን የገቡት ብዙዎቹ ኢትዮጵያውያን ስደተኞች፡፡ እዚያ የታወቁ ሁለት አሸጋጋሪዎች አሉ፡፡ በአካል አታገኟቸውም፡፡ ስልካቸውን ከሀገር ሳትወጡ ይዛችሁ መሄድ አለባችሁ፡፡ አለበለዚያም ጣልያን የገባ ሰው ሊነግራችሁ ይገባል፡፡

አንዳች ሰዋራ ሥፍራ ተደብቃችሁ በስልክ ታገኟቸውና የጉዞ ዋጋ እና ቀን ትነጋገራላችሁ፡፡ እነርሱም ገንዘቡን ይዛችሁ የምትመጡበትን ቦታ እና ቀን ይነግሯችኋል፡፡ በተባላችሁት ሌሊት እቦታው ስትደርሱ እንደ እናንተ በቀጠሮ የመጡ ሌሎች ስደተኞችን ጨምረው በጭነት መኪና ወደ ሊቢያ ድንበር ትወሰዳላችሁ፡፡ ጉዞው ሌሊት ሌሊት፣ ያውም አብዛኛው በእግር፣ ጥቂቱ ደግሞ በመኪና ስለሆነ ከሃያ ቀን እስከ አንድ ወር ይፈጃል፡፡

ሊቢያ ድንበር ስትደርሱ የሱዳን አሸጋጋሪዎች ለሊቢያ አሸጋጋሪዎች ያስረክቧችኋል፡፡ ዋጋ ተነጋግራችሁ አሁንም ጉዞ ትጀምራላችሁ፡፡ ግማሹን በእግር ግማሹን በፒክ አፕ መኪና፡፡ ደረቅ ዳቦ እና ውኃ ይሰጣችኋል፡፡ መንገድ ላይ የሚሞቱ ልጆች ይኖራሉ፡፡ አሸዋውን ማስ ማስ አድርጎ በመቅበር ጉዞ መቀጠል ነው፡፡

«በእግር ወይንም በመኪና ስትጓዝ በእንጨት የመስቀል ምልክት የተሠራበት ነገር ካየህ እዚያ ቦታ አንድ አበሻ ስደተኛ ተቀብሯል ማለት ነው፡፡» ብሎኛል ጣልያን ያገኘሁት ልጅ፡፡ «ሰው ከታመመ እንደ በሽታው ነው፡፡ መጠነኛ ከሆነ በድጋፍ ይሄዳል፡፡ ከባድ ከሆነ ግን ቁርጥ ወገን ያስፈልገዋል፡፡ ከቡድኑ ከተቆረጥክ ችግር ስለሚያጋጠምህ አንዳንዱ ትቶህ ይሄዳል፡፡ ብዙ ጊዜ ግን የቂርቆስ ልጆች ይተዛዘናሉ፡፡ እንዲያውም

ከቂርቆስ ልጅ ጋራ አብረው ቢሰደዱ
ቢያገኝም ያበላል ቢያጣም ያዝናል ሆዱ

ገድለ ዜና ማርቆስ የያዛቸው መረጃዎችና ሁነቶች

ገድለ ዜና ማርቆስ የያዛቸው መረጃዎችና ሁነቶች


ይህ ጽሑፍ በ2001 ዓም የኢትዮጵያ ፊሎሎጂ ማኅበር ባዘጋጀው 3ኛ ዓመታዊ ዐውደ ጥናት ላይ የቀረበ ነው፡፡


መግቢያ

በግእዝ ቋንቋ የተጻፉ ከ200 በላይ ገድላትን እስከ አሁን ለማየት ዕድል ገጥሞኛል፡፡ የገድላቱ አጻጻፍ ተመሳሳይ የሆነ «ቅርጽ» /format/ እና ተመሳሳይ የሆነ «ፍሰት» /Flow/ የሚከተሉ ሆነው አግኝቻቸው ነበር፡፡ በዚህ ጽሑፍ «ቅርጽ» የምለው የገድሉ ባለቤት ታሪክ፣ ገድል፣ ቃል ኪዳን፣ ተአምር እና መልክዕ የሚጻፍበት መንገድ ማለቴ ነው፡፡ በአብዛኞቹ ገድሎች መጀመሪያ የሃይማኖት መሠረት የሚሆነው ምሥጢረ ሥላሴ እና ምሥጢረ ሥጋዌ በመግቢያነት ይቀርባል፡፡ ከዚያም የቅዱሱ ትውልድ ይገለጣል፤ ቀጥሎም ገድሉ ይከተላል፤ ከዚያም የተሰጠው ቃል ኪዳን ይጻፋል፤ በመጨረሻም ተአምሩ እና መልክዑ ይቀርባል፡፡

«ፍሰት» የምለው ደግሞ የታሪኩ ቅደም ተከተል የቀረበበትን መንገድ ነው፡፡ ታሪኩ ከየት ተነሥቶ፣ በየት በኩል አልፎ፣ የት ይደርሳል የሚለው ነው፡፡ በብዙዎቹ ገድሎቻችን ከቅዱሱ ወላጆች ይጀምርና አወላለዱን ከገለጠልን በኋላ የአካባቢያዊ እና የትምህርታዊ ዕድገቱን፤ ገዳማዊ ሕይወቱን፣ የተቀበለውን መከራ፤ ዕለተ ዕረፍቱን ነው የሚተርክልን፡፡

የገድለ ዜና ማርቆስ አቀራረብ ግን ከዚህ ከተለመደው መንገድ ወጣ ያለ በመሆኑ ስለ ገድላት ያለንን ዕውቀት የሚያሳድግ ብቻ ሳይሆን ተጨማሪ መረጃም የሚሰጥ ሆኖ አግኝቼዋለሁ፡፡ ገድሉን ለማንበብ ለመጀመሪያ ጊዜ ዕድል ያገኘሁት የዛሬ ስድስት ዓመት በደብረ ብሥራት ዜና ማርቆስ ገዳም ከሚገኘው ዕቃ ቤት ነበር፡፡ ነገር ግን በዚያ ጊዜ ለረዥም ሰዓታት ማንበብ እና ከሌሎች ነገሮች ጋር ለማዛመድ የቦታው ሁኔታ አላመቸኝም ነበር፡፡ በኢትዮጵያ ማይክሮ ፊልም ማኑስክሪፕትስ ቤተ መጻሕፍት የሚገኘውን የማይክሮ ፊልም ቅጅ ለማንበብም በወቅቱ የማተሚያ መሣሪያው በመበላሸቱ በመብራት ረዥም ሰዓት ማጥናት አልተቻለም ፡፡ በዚህ መካከል ግን ገድለ ዜና ማርቆስን ገዳሙ አሳተመው፡፡ በመሆኑም ተረጋግቶ ለማጥናት ዕድል ተገኘ፡፡

ገድለ ዜና ማርቆስ ከብዙዎቹ ገድሎች የሚለይባቸው ነጥቦችን በዝርዝር ማየቱ ገድሉ በሃይማኖት፣ በታሪክ፣ በመረጃ እና በሥነ ጽሑፍ ዘርፎች ያለውን ቦታ ያመለ ክታል፡፡ የቤተ ክርስቲያናችንን ገድላት ያለ ጥልቅ ጥናት ከመተቸትና ታሪክ የማይሽረው ስሕተት ከመሥራትም ያድናል በማለት እንደሚከተለው ቀርቧል፡፡

Thursday, December 18, 2014

ጲላጦስ : Daniel Kibret Views

ጲላጦስ Wednesday, March 31, 2010 
By DanielKibret.com

ሚያዝያ 14 ቀን 2000 ዓ.ም በኢትዮùያ አየር መንገድ የበረራ ቁጥር ET 603 ከዱባይ ወደ አዲስ አበባ በመምጣት ላይ ነበርኩ፡፡ ሻርጅያ በተባለው ከተማ አንድ ኢትዮ ጵያዊ የጠየቀኝን ጥያቄ አወጣለሁ፣ አወርዳለሁ፡፡ ወቅቱ በኢትዮጵያ ክርስቲያኖች ዘንድ ‹ሰሙነ ሕማማት› የሚባለው ነው፡፡ ሚያዝያ 17 ቀን ስቅለት ከሁለት ቀናት በኋላ ደግሞ የትንሣኤ በዓል ይከበራል፡፡

ያ ኢትዮጵያዊ ወዳጄ፡- ‹‹መስፍኑ ጲላጦስ ክርስቶስን ለምን አሳልፎ ሰጠው?›› የሚል ጥያቄ ነበር ያነሣልኝ፡፡ ለጊዜው ይኾናል ያልኹትን ማብራሪያ ሰጠኹት፡፡ በኋላ ግን እኔው ራሴ በነገሩ ማሰላሰሌን ቀጠልኹ፡፡